Funny article by the well known Ethiopian writer Bewketu Seyoum

አዝናኝ ወግ…
.
የዳያስፖራዎች ቤት ግብዣ :-
.
ከዘፋኞች ቡድን ጋር አሜሪካ በገባን ማግስት ዘፋኞች በዶላር ከበሩ፡፡

እኔ አጥብቄ ተቸገርኩ፡፡

በወይዘሮ የሺሻ-ወርቅ ናይት ክለብ ውስጥ፤ ፋሲል ደመወዝ የጣውላ ክላሹን አነግቶ “አረሡት የሁመራን መሬት” ብሎ ዘፍኖ ሁመራን ለመሸመት የሚበቃ የሽልማት ዶላር ይዞ ሲወርድ እኔ ግጥም ለማንበብ ወደ መድረክ እወጣለሁ፡፡

Bewketu

ከዚያ በግጥም ደብተሬና በእኔ መሃል የቆመውን ወፍራም የሺሻ ጭስ ባይበሉባዬ ገለል አድርጌ…

“ዓለማዊ ልቤ ለበሰልሽ ዳባ ምናኔ ተመኘ
በእናቴ ቀብር ላይ የጠፋብኝ እምባ ፊቴ ላይ ተገኘ“
…ብየ ስጀምር አያስጨርሱኝም፡፡

“ምናኔ ደሞ ምንድነው”? ትለኛለች ከጥግ ቁጭ ብላ ሺሻ የምትጠባ ደንበኛ፡፡

ብልጭ ይልብኛል ! ግጥሜን ላንብብ ወይስ አንቺን አማርኛ ላስተምር?

“አቦ ይሄ ልጅ ያስቃል ሲባል አልነበረ እንዴ ? ምንድነው እዚህ ”ቀብር“ ምናምን እያለ የሚያለቃቅስብን ?”ይላል ሌላው የሚወረወር ነገር ባካባቢው እየፈለገ፡፡

ከጥቂት ጊዜ በኋላ ከኢትዮጵያ ያስመጣኝ ፕሮሞተር በኔ ተስፋ ቆረጠ፡፡ ጥረህ ግረህ ብላ ብሎ ጥሎኝ ጠፋ፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ምግብ አማርጥ የነበርኩት ሰውዬ አሜሪካ ውስጥ ያለ ፈቃዴ በተከታታይ እፆም ጀመር፡፡

ጠዋት የቤቴን በር ስከፍት ከነ ጃንቦ ጆቴ ክፍል መአት ዓይነት የፕላስቲክ አገልግል፤ የሰርዲን ጣሳ፤ ድርብ ሰረዝ የመሰለ በርገር፤ እንዲሁም የቢራ ጠርሙስ እየተጠረገ ሲወጣ አያለሁ፡፡

ሲብስብኝ ማንኛውንም የምሳ ግብዣ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ መቀበል ጀመርኩ፡፡

ዘፋኞቹ ”ተጋባዡ ገጣሚ“ በማለት ይፎትቱኝ ጀመር፡፡

አንድ ቀን ቨርጂንያ አውራ ጎዳና ዳር ቆሜ በጥሞና ሳሰላስል ፊቴ ላይ የሚታየውን ጥልቅ ጥሞና የተመለከተ ሰው ስለ ቀጣይ ያገራችን እጣ ፈንታ እንጂ ስለ ቀጣዩ ምሳ እያሰበ ነው ብሎ አይገምትም፡፡

”ሃይ በእውነቱ“ የሚል የሴት ድምጽ ካሳቤ አባነነኝ ፡፡

አንዲት ያገሬ ልጅ መኪናዋን አቆመችልኝ፡፡

ትንሽ ከተደናነቅን በኋላ ”ለምን ምሳ አብረን አንበላም?“አለቺኝ፡፡

ገና ”ለምን ምሳ… “ የሚለው አርፍተ ነገር ባየር ላይ እያለ መኪናዋን ከፍቼ ከኋላ ወንበር ቁጭ ብያለሁ፡፡

ትንሽ እንደ ሄድን መኪናዋን ካንድ ጥግ አቁማው የሆነ ዐራት ማእዘን ሰውዬ ገብቶ አጠገቧ ተቀመጠ፡፡

ከዚያ ዞር ብሎ “የማን አባቱ ጉቶ ነው” በሚል አይነት ገላመጠኝ ፡፡

ወድያው ግን በድጋሚ ከተመለከተኝ በኋላ
“አጅሬ! አንተነህ እንዴ?ለመሆኑ ወደ ሥነጽሁፍ ዓለም እንዴት ገባህ“ እያለ በባዶ ሆዴ ያደርቀኝ ጀመር፡፡

ቤት ገብተን ልጅት ምሳ ለመሥራት ወደ ጓዳ ገባች፡፡

ሰውየው የፍቅርና የትዳር ታሪኩን ባጭሩ ለሁለት ሰዓት ያህል ተረከልኝ፡፡

አዲሳባ ውስጥ በፍቅር እንደኖሩ፤ ከዚያ እሱ ወደ አሜሪካ እንደተሰደደና እሷን በስንት ውጣውረድ እንዳመጣት ነገረኝ፡፡ በቅጡ አልሰማሁትም፡፡

ከሰውየው ትረካ በላይ ጥርት ብሎ የሚሰማኝ ከጓዳ የሚመጣው የመክተፍያ ድምጽ ነበር፡፡

ልጅቷ በያይነቱ ሠርታ ጨረሰች፡፡ ግን ቶሎ አልቀረበም፡፡

እኔን ራብ እየሞረሞረኝ ባልና ሚስቱ ስለኣቀራረብ ስታይል ይራቀቃሉ፡፡

“ስንግ ቃርያው የሚቀመጠው ከቲማቲሙ በስተቀኝ በኩል ነው በስተግራ በኩል ነው”? በሚለው ዙርያ ለሃያ ደቂቃ ያክል ተከራከሩ፡፡

እኔ ወደ ማእዱ ለመሄድ ትንሽ ሲቀረኝ ማእዱ ከፊቴ ቀረበ፡፡

”ይገርምሃል ለመጀመርያ ጊዜ ሲዲህን የሰማሁት ደሳለኝ ቤት ሆኜ ነው” አለችኝ ከጠረጴዛው ላይ ብርጭቆ የሞላ ውሀ እያስቀመጠች፡፡

”ደሳለኝ? ደሳለኝ ማን ነው?“አለ ሰውየው የህጻን ብርድልብስ የሚያክል እንጀራ ሰሀኔ ላይ እያነጠፈ፡፡

”ደሳለኝ፡፡ ተከራይቶ የሚኖር ልጅ ነበር፤ እኛ ግቢ”
”ኦኬ ምን ልትሠሪ ቤቱ ገባሽ?“ ባሉካ ባረቀ፡፡

”ቲቪ ላይ ነዋ ! የደሳለኝ ብቸኛ ሀብቱ ግዙፍ ቴሌቪዥኑ ነበር፡፡ ይገርምሀል ቤቱ ውስጥ ወንበር እንኳ አልነበረውም” አለች ወደኔ ዞራ፡፡

“ወንበር ከሌለው ታድያ ምን ላይ ተቀምጠሽ ቲቪውን ዓየሽው?” ሰውየው አፈጠጠ፡፡

“እምም አልጋው ጫፍ” አለች ፈገግታዋ እንዳያመልጣት ከንፈሯን እየጨቆነች፡፡

ሰውየው ለመደባደብ ያሟሙቅ ጀመር፡፡

ብድግ ብዬ ”ተው እንጂ! ነውር ኣይደለም እንዴ?” ምናምን እያልኩ በማሃላቸው ገባሁ፡፡

“ነውር ኣይደለም እንዴ? አትሊስት ምሳዬን እስክበላ ድረስ ለምን አትታገስም?“ አልኩ በልቤ፡፡

”አሜሪካ እንዳለህ አትርሳ፡፡ ጫፌን አትነካኝም!“ አለች ከመጤፍ ሳትቆጥረው፡፡

እውነቷን ነው፤ አሜሪካ ውስጥ የሴትን ጫፍ መንካት ትልቅ ወንጀል ነው፡፡ ወንዶች ንዴታቸውን የሚወጡት ግድግዳ በቴስታ በመምታትና የመኪና ጎማ በካልቾ በመጠለዝ ነው፡፡

ሰውየው በንዴት አረፋ እየደፈቀ ዞር ሲል ከግድግዳ የተሻለ ንዴቱን ማስተንፈሻ ተመለከተ፡፡

ቁልቁል ዐየኝ፡፡

ቀጥሎ የተከሰተው ብዙ ነገር ትዝ አይለኝም፡፡
ብቻ…

“አቦ ወደዛ ዞርበልልኝ” ሲልና የመጥረቢያ ዛቢያ የመሰለውን ክርኑን ወደ አንገቴ ሲሰነዝር ትዝ ይለኛል፡፡

አንገቴ ወደ ቀድሞው ጤንነቱና ውበቱ ለመመለስ ላንድ ሳምንት ያህል የፒትልስ ሹራብ ኰሌታ የመሰለ ጄሶ ድጋፍ ማግኘት ነበረበት፡፡

እና እስከዛሬ ድረስ ”አንገት ከሚሰበር ባይበላስ ቢቀር“ የሚለውን የቴዲ አፍሮ ዘፈን በሰማሁ ቁጥር ይሄ ልጅ የኔን ታሪክ ማን ነግሮት ይሆን ? እላለሁ፡፡

Bewketu Seyoum is a prolific Ethiopian poet and writer. He has published books and collections of CDs as well as wrote numerous articles .
.
Source –  Bewketu Seyoum -Face Book

 

Yohannes Ayalew

Related Posts

Leave a Reply

Read also x